Monday, October 29, 2012


   ድንግል ማርያም የውርስ ኃጢአት ይመለከታታልን ?  ክፍል 6
    ድንግል ማርያም የውርስ ኃጢአት ይመለከታታልን?
ከዚህ ቀደም ባቀረብናችው ጽሁፎች  እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም  የጥንተ አብሶ ፍዳ እንደ ማይመለከታት ቅዱሳን አባቶቻችን የተናገሩትን መመልከት ጀምረን ነበር በዚህ ጽሁፋችንም ቀጣዩን ክፍል እንመለከታለን  አምላካችን ልዑል እ ግዚአብሔር የእናቱን በረከት ረድኤት ያሳድርብን አሜን
  ቅዱስ  ኤራቅሊስ  በሃይማኖተ  አበው ምዕራፍ  48 ቁጥር 31  ስለ እመቤታችን ንጽህና ሲመሰክር እንዲህ ይላል 
     « ኢያእመረ እስመ ዘተፈጥረት እምነ ጽቡር ጽሩይ ትከውን  መቅደሶ ለእግዚአብሔር »ትርጉም « የእግዚአብሔር መቅደሱ ማደርያው ትሆነው ዘንድ ከንጹህ አፈር (ዘር)የተፈጠረች  መሆኗን አላወቀም  »
ታላቁ የቤተክርስትያን አባት ቅዱስ ኤራቅሊስ  ይህንን ኃይለ ቃል የተናገረው አረጋዊ ካህን ዮሴፍ ለእመቤታቸን አገልጋይ ሆኖ የታጨለትን ምሥጢር በተረጎመበት ክፍል ነው  ።በእርግጥ አረጋዊ ዮሴፍ ለእመቤታችን ለምን እንደታጨ አላወቀም ነበር እርሷም ትንቢት የተነገረላት ሱባዔ የተቆጠረላት አምላክን በድንግልና ጽንሳ በድንግልና የምትወልድ ከመርገመ አዳም  ከመረገመ ሔዋን የተለየች መሆኗን አላወቀም ነበር። ነገሮችን መረዳት የጀመረው መልአኩ ካረጋጋው በኃላ የተለያዩ ምልክቶችን አይቶ ነው ።ሊቁም ይህንን ሲያስረዳ « የእግዚአብሔር መቅደሱ ትሆነው ዘንድ ከንጹህ አፈር የተፈጠረች መሆኗን አላወቀም « 
        ይህም አገላለጽ ወላዲተ አምላክ ስትፈጠር ጀምሮ ንጽህት ቅድስት መሆኗን ያስርዳል ዮሴፍ ማንነቷን ከማወቁ በፊት እንደማናቸውም አንስት ከአዳማዊ እዳ በደል ያልተለየች ሴት መስላው ነበር ሁሉን የተረዳው ቆይቶ ነው ድንግል ማርያም ግን ሊቁ እንደተናገረው ተፈጠሮዋን በተመለከተ « ከንጹህ አፈር « በማለት ንጽሐ ጠባይዋ ያላደፈባት ያልጎደፈባት ገና በማህጸን አጥንት  ሰክቶ ሲፈጥራት በንጸህና የጠበቃት ስለሆነች ከንጹህ አፈር የፈጠራት በማለት ተናገረ ። ድንግል የአምላካችን አማናዊት መቅደስ ናት  እንደ ደንግል ማርያም የእግዚአብሔር ማደርያ የሆነ ማንም የለም በሌሎቹ ሁሉ ቢያድር በጸጋ ነው  በእመቤታችን ግን በኩነት ሰው በመሆን በተዋህዶ ነው ያደረባት ስለዚህም አማናዊት መቅደስ ናት ።የእግዚአብሄር መቅደስ ደግሞ በእውነት ንጹሕ ነው ኃጢአት የማይስማማው ንጹሐ ባህርይ የሆነ መለኮት ንጹህ ማደርያን ይፈልጋልና ።
       ከሊቁ ከቅዱስ ኤራቅሊስ ንግግር ልናስተውለው የሚገባን መሰረታዊ ነጥብ አለ ይህም ድንግል ማርያምን በንጽህና ፈጠራት አለ እንጂ ከፈጠራት በሁኃላ አነጻት አላለም  አንዳንድ አደናጋሪዎች ወላዲተ አምላክ ክብር ምስጋና ይግባትና አዳማዊ መርገም በብስራተ መልአክ ጠፋላት እያሉ ለማሳሳት ይሞክራሉ ይህ ግን አላዋቂነት ነው ቅዱሳን አበው በመንፈስ ቅዱስ እየተመሩ ያስተማሩትን ትምህርት ማስተባበል ነው ደግሞስ መርገም በብስራተ መልአክ የሚጠፋ ከሆነ መላእክት ያበሰሯቸው ሁሉ መርገመ አዳም መርገመ ሔዋን ጠፍቶላቸዋል ማለት ነው ? ይህስ ከሆነ የአምልክ መውረድ  መወለድ ሰው መሆን ሰጋውን መቁረስ ደሙን ማፍሰስ ለምን አሰፈለገው ? በክርስትና አስተምሮ መሰረት  የእመቤታችን የቅድስት ማርያም ነገር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ከምሥጢረ ድህነት ጋር የተያያዘ ነው ስለዚህም ነው ስለእርሷ የምንናገረውን ነገር ልንጠነቀቅ የሚገባን ።ሊቁ ቅዱስ ኤራቅሊስ ከንጹህ አፈር ተፈጠረች ማለቱ የሚጠቁመን ሌላ ነጥብ ደግሞ በጥንተ ተፈጥሮ ስንመለከት ከአፈር በቀጥታ የተፈጠረ አባታችን አዳም ብቻ ነው  ሌሎቹ አዳማዊያን መሰረታቸው አፈር ቢሆንም የተፈጠሩት በውልደት ነው  ድንግልን ግን ከንጹህ አፈር ተፈጠረች አላት ይህም  ምሳሌ ነው በቁሙ አፈር ንጹህ እና ቆሻሻ ተብሎ  አይደለም ነገር ግን  በዚህ አገላለጽ  በአፈር የተመሰለ የሰው ልጆች ሰውነት ነው በቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ እንደተባለ
             «አፈር  ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ » ዘፍ 3 ፡19 
 ከሌሎች የአፈር አይነቶች ተለይቶ ተዋስያን በሌሉበት  በንጹህ አፈር የተመሰለ  መርገመ አዳም መርገመ አዳም ያልነካው የእመቤታችን ሰውነት ነው ምንም እንኳን አምላክን ብትወልደውም እንደ ሰው ሁሉ  ተፈጥሮዋ እንደ አዳማዊያን ከአፈር ነውና ሰለዚህም ቅድስት ቤተክርስትያን የእውነተኞቹን ደጋግ አበው ምስክርነት ከቅዱሳት መጻህፍት ጋር አስተባብራ  ወላዲተ አምላክ መርገመ ስጋ መርገመ ነፍስ የሌለባት የጥንተ አብሶ ፍዳ የተለየች መሆኗን አበክራ ታስተምራለች
                                                      ይቆየን
     ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከንጽህናዋ በረከት ረድኤት ያሳትፈን አሜን

1 comment:

  1. ቃለ ሕወት ያሰማልን! ለብዙ መናፍቃን መልስ ይሆናል ብዬ አስባለሁ በተጨማሪም ይህ ጥያቄ በአእምሮአቸው ለምመላለስባቸው ለምእመናን ጭምር ::

    ReplyDelete